በተለያዩ የህይወት ሁነቶች ውስጥ ነፍሴ ተጠምዳ ቀናቶች ሲበሩ አስተውላለሁ። ለመኖር ያስፈልጋሉ ብዬ የማምንባቸውን ተግባራት ስተገብር ነገ ዛሬ እየሆነ አያለሁ። በዚህ ሁሉ ውስጥ ግን ሁል ጊዜ ለ ነፍሴ ላስታውሳት የምፈልገው አንድ እውነት አለ እርሱም በኢየሱስ የማያልቅ ፍቅር መወደዷን ነው። ይህን ፍቅር መረዳት የህይወትን አቅጣጫ እለት ተዕለት እንደሚቃኝ እና እንደሚቀይር አምናለሁ። ምንም እንኳን ለ ቅዱሳን ስለ ኢየሱስ ፍቅር ማሰብ እና መገረምን የሁል ጊዜ ህይወታቸው እና ለሌሎች የሚያካፍሉት እውነት ቢሆንም በሰው መረዳት ልክ ታውቆ የሚያበቃ ባለመሆኑ መንፈስ ቅዱስ በተለያዩ አጋጣሚዎች እና ሁኔታዎች ውስጥ የኢየሱስን ፍቅር እያብራራ ያስገርመናል። ለእኔ ስለዚህ ፍቅር ሆነ ብዬ እንዳስብ ከሚያደርጉኝ ሁኔታዎች መሀከል የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስ መወለድን የማስብበት ወቅት ነው። የኢየሱስን ወደ ምድር መምጣት በማስብበት ጊዜ የፍቅሩን ልክ ያሳየኛል። ሊደረስበት በማይቻል ከፍታ ያለው አምላክ ፍጥረቱን ሊታደግ የወረደበት ምክንያት ፍቅር ነው! ዛሬ ባለሽበት ሁኔታ ውስጥ ይህን ጥልቅ ፍቅር እንድታስቢ አበረታታሻለሁ።
አዳኝሽ ኢየሱስ ያገኘሽ አንቺ ወጥተሽ ሳይሆን እርሱ ወርዶ ነው!
ይህ በዘመናት ሁሉ አስገራሚነቱን ጠብቆ የሚኖር እውነት ነው። ብቃትሽን ሳይሆን እርሱ ላንቺ ያለውን የማይገመት ፍቅር ያሳየበት መንገድ ነው። አምላክን ሰው እንዲሆን ባደረገው ፍቅር ተመርጠሻል፣ አማኑኤል ካንቺ ጋር ሊሆን ያለመስፈርት ወርዶልሻል! ይህ እውነት በየእለቱ በዝማሬ እና በስብከት ሲቀርብ ሊለመድ ቢችልም ላንቺ ግን ያልቀለለ ሚስጥር ነው! ከድቅድቅ ጨለማ ወደ ሚደነቅ ብርሀን የመጣሽበት መንገድ፣ ከ ባርነት ህይወት ወደ ልጅነት እና የእግዚአብሔር ወራሽነት የተሸጋገርሽበት መንገድ፣ እግዝአብሔርን አባ አባት ብለሽ እንድትጠሪው ያስቻለሽ ሚስጥር ነው። ዛሬ በዚህ ሀሳብ አምላክሽ ላንቺ ያለውን ታላቅ ፍቅር እያየሽ በምስጋና እና አምልኮ ቀንሽን ጀምሪ። ደግሞም በፀጋው የተመረጠው ማንነትሽ ምን ያህል ለዚህ ታላቅ ፍቅር ተገቢውን ምላሽ ሰጥቶ እንደሆን ገምግሚ። ዘላለማዊ ፍቅሩና አብሮነቱ ዛሬም ከአንቺ ጋር ነው ልታስቢው ራስሽን ባቀረብሽበት ልክ በፍቅሩ ያስገርምሻል! አማኑኤል ከአንቺ ጋር ነው
ጸሎት
ጌታ ሆይ በማይቆጠር ፀጋህና ፍቅርህ ስላሰብከኝ አመሰግንሃለሁ! የሰው ልጅ ሆነህ መምጣትህ ሊለመድ የማይችል እውነት እና ለኔ ያለህን ፍቅር ያየሁበት መንገድ ነው። ደግሞ ይህን ፍቅር እለት እለት እንድረዳው እና በህይወቴ እንድመላለስበት ፀጋህ ይርዳኝ አሜን!