Friday, 31 December 2021 00:00

ቀን 10:- እንደተራ ሰው

Written by

ትልቁ ሕልምሽ ምንድነው? ሕልምሽ ዕብደት መስሎ ተሰምቶሽ ያውቃል? ሁሌም ልታሳኪው እንደምትችዪ ይሰማሻል? በቀን ምን ያህል ጊዜ “እንዴት ሊሆን ይችላል?” ብለሽ ትጠራጠሪያለሽ? ሸክሙ ከባድ ስለሆነ ስንት ጊዜ ትቼው በቃ “ተራ” ሰው ብሆንስ ብለሽ አስበሻል? እኔ ብዙ ጊዜ እንደዚህ አስቤያለሁ፡ ትልቅ ሸክም ስለሆነ በዚያ ፋንታ ተራ ሰው ብሆን ብያለሁ። 

ሉቃስ 1፡28-35 ላይ በመልዓኩ ገብርዔልና በማርያም መካከል የተደረገ ደስ የሚል ንግግር እናገኛለን። ይህንን ክፍል በደንብ እናውቀዋለን፣ ግን ማርያም እንዴት እንደተቀበለችው ለማየት እስኪ ቀስ ብለን እናጢነው። ከማንኛውም ሰው እንደሚጠበቀው ማርያም ያልተጠበቀ ሰላምታውን ስትሰማ ደነገጠች (ቁጥር 29)፤ ከዚያም መልዓኩ አትፍሪ እንዳላት ስናይ እንደፈራች ማወቅ እንችላለን (ቁጥር 30)፤ በመጨረሻም አሁን ባለሁበት ሁኔታ ይህ እንዴት ሊሆን ይችላል ብላ ጠየቀች። 

ይህ ከማንኛውም ሰው የሚጠበቅ ምላሽ አይደል? ድንጋጤ፣ ፍርሃት፣ እንዴት እንዲህ ዓይነት ታላቅ ዕቅድ በእኔ ይሆናል ብሎ መጠየቅ። 

መልዓኩ በቁጥር 35 ላይ ደስ የሚለኝን ምላሽ ሰጠ፡ “መንፈስ ቅዱስ በአንቺ ላይ ይመጣል፤ የልዑልም ኃይል ይጸልልልሻል” - ይህ ቀላል ንግግር አይደለም። ማርያም ምንም እንኳን እንደሌሎቻችን ሰው ብትሆንም የእግዚአብሔርን ልጅ ልትወልድ የቻለችው በዚህ ምክንያት እንደሆነ አምናለሁ። 

“ይጸልልልሻል” የሚለውን ቃል ትርጉም ስንመለከት “መጠበቅ፣ መጋረድ፣ በጠባቂ ተጽዕኖ ሥር ማድረግ” የሚል ሃሳብ ነው። ይህ ማለት ማርያም በመንፈስ ቅዱስ ጥበቃ ሥር፣ በእርሱ ተጋርዳና ተከልላ እንደምትኖር ማረጋገጫ ተሰጥቷታል። 

እኛም ይህ ማረጋገጫ አለን! ኢየሱስ መንፈስ ቅዱስን እንደሚልክልን ነግሮናል (ዮሐንስ 14፡16፣ 26)፤ የመዳናችን ማረጋገጫ ማህተማችንም እርሱ ነው። (ኤፌ 1፡13-14) 

ማርያምን ኃይል የሰጠው መንፈስ ቅዱስ በእኛ ውስጥ ከሆነ ለመውለድ የማይቻል ምን አለ? የትኛው ሕልም ለመሸከም አዳጋች ይሆናል? ምን ዓይነት ዓላማ የማይፈጸም ይሆናል? 

 

ጸሎት

በታላቁ እግዚአብሔር ጥበቃና ክለላ ሥር ለመሆን ራሳችንን ሁልጊዜ እያቀረብን በውስጣችን ያስቀመጠውን ሕልም እንድንፈጽም እጸልያለሁ። 

መልካም ገና!

white-200.png

Serving Ethiopian women by encouraging and exemplifying vulnerable, thought-provoking conversations around the Gospel of Jesus Christ, the mission of the
Church, and the life of a Christian.

Address
:
Golagul Tower
Addis Ababa, Ethiopia

Emailinfo@selahethiopia.org
selahforethiopia@gmail.com

Follow Us

Subscribe to emails from Selah

We have officially launched our website and all our social media platforms. Please join us, follow, and share. Subscribe to our newsletter bringing you regular updates, resources, and everything in between!

Copyright © 2023 Selah Ministries.
Address: Addis Ababa, Ethiopia 
Emailinfo@selahethiopia.org