Sunday, 25 October 2020 23:27

ዕድለኛ አይደለሁም

Written by

9ኛ ክፍል እያለሁ አንድ ቀን አባቴ ከትምህርት ቤት መልስ እያደረሰኝ ሁሌ እንደምናደርገው ልብ ለልብ እየተጫወትን ነበር። (እየቀለድኩ ነው) ወላጆቼ 6 ልጆቻቸውን ሲያሳድጉ ቤታችንም ሆነ ከቤት ወጪ ሲያደርሱንና ሲመልሱን ጸጥታና ተረጋግቶ መነጋገር የሚያጋጥመን በጣም አልፎ አልፎ ነው። ሁላችንም ብዙ ጉዳዮችን በአንድ ጊዜ ስለምናወራ አሁን እንኳ አንድላይ ስንሰበሰብ ላልለመደው ሰው ከፍተኛ ትንግርት የሆነ ትርምስ ነው። በዚያን ቀን ግን እህቶቼና ወንድሜ በምን አጋጣሚ እንደሆነ ባላውቅም አብረውን ስላልነበሩ ከፓፕስ (አባቴ) ጋር ለማውራት ቻልን። በቀኔ ውስጥ ስላጋጠመኝ አንድ መልካም ነገር ነገርኩትና “ለነገሩ ማክሰኞ የዕድል ቀኔ (my lucky day) ነው” ብዬ ቀጠልኩ። የተወለድኩበትና ከዚህ በፊትም የምቆጥራቸው ብዙ መልካም ነገሮች ማክሰኞ ቀን እንዳጋጠሙኝ በከፍተኛ ደስታ ሰፊ ማብራሪያ ሰጥቼ ልክ እንደጨረስኩ አባቴ መለስ ብሎ “ይህ ጣዖት አምልኮ ነው” ሲለኝ የተሰማኝን ድንጋጤ እስከዛሬ አስታውሰዋለሁ። አባቴ ቀጥሎም በሕይወታችን ለሚመጡ ማንኛውም መልካም ነገሮች እንደምክንያት የምናቀርበው ክስተቱ የተፈጠረበት ቀን፣ የለበስነው ልብስ (“lucky color”)፣ ከምንወደው ሰው ጋር በመሆናችን ወዘተ... ከሆነ ለእግዚአብሔር የሚገባውን ክብር ለሌላ እየሰጠን እንደሆነ ነገረኝ። ሁሌ ከማስታውሳቸው ትምህርቶች አንዱ ነው። 

በምን መልኩ ይሆን ለእግዚአብሔር የሚገባውን ክብር ለሌሎች ወይም ለራሳችን ስንሰጥ የምንገኘው? በተደጋጋሚ ፈተና የሚሆንብኝ ነገር በተለይ ክርስቲያን ካልሆኑ ወይም የእግዚአብሔርን ሉዓላዊነት ከማይቀበሉ ሰዎች ጋር በሚኖር ውይይት ነው። አንድ መልካም ነገር በሕይወቴ ለምን እንደሆነ ሳስብ ከእግዚአብሔር እጅ የተቀበልኩት ነገር መሆኑን ምንም ጥርጥር የለኝም፤ ግን ይህንኑ ጉዳይ በእግዚአብሔር ላይ ተመሳሳይ እምነት ለሌላቸው ሰዎች ሳካፍል “ይህንን ያደረገልኝ እግዚአብሔር ነው” ብዬ በግልጽ ከመመስከር ይልቅ እንደዕድል፣ ወይም በእኔ ጥረት እንደተገኘ ነገር አድበስብሼው ሳልፍ ራሴን አገኘዋለሁ። ምንም እንኳን የእኛ ማኅበረሰብ ኃይማኖተኛ ቢሆንም ግን ከጊዜ ወደጊዜ እያደገ ካለው ዓለማዊነት (secularism) የተነሳ ተመሳሳይ እምነት ከማይጋሩ ሰዎች ጋር ስንነጋገር የእግዚአብሔርን ስም ለመጥራት፣ ስላደረገልን ነገር በግልጽ ለመናገር እናመነታለን። በሕይወታችን ያለ ማንኛውም መልካም ነገር የመጣው በሌላ ምክንያት ወይም በራሳችን ጥረትና ጉብዝና እንደሆነ ካሰብን ለእግዚአብሔር የሚገባውን ክብር ለሌላ እየሰጠን ነው። አንዳንዴ ደግሞ የውሸት ትኅትናን በመምረጥ መልካም ነገሮቻችንን ሰዎች ሲያነሱ “አይ እሱ እኮ ምንም አይደለም” ብለን እናልፈዋለን - ይህን በማድረግ የእግዚአብሔርን ታላቅ ተዓምርና በጎነቱን እናሳንሳለን። 

በዚህ ምድር ላይ ያለን ዋና ተልዕኮ ለሌሎች የእግዚአብሔርን መልካምነት መመስከር፣ ታላቅነትና ጽድቁን ማሳየት ነው። በሕይወታችን የሚታዩት ከእግዚአብሔር የተቀበልናቸው መልካም ነገሮች ለዚህ ተልዕኮ መንገድ የሚከፍቱ ዕድሎች ናቸው። የእግዚአብሔርን ተዓምራትና የእርሱን በጎነት እየቆጠርን እርሱን ስናመሰግን ልባችን በሌላ ምስጋና ይሞላል፣ የሚትረፈረፍ ደስታና አመስጋኝነት መለያችን ይሆናል። ሰዎች ሕይወታችንን በማየትና (በሥራ፣ በቤተሰብ፣ በሀብት፣ በጓደኞች፣ በባህሪያችን፣ በትምህርታችን ... ሊሆን ይችላል) እግዚአብሔር ያሳካልንን ነገሮች በመቁጠር “ውይ እንዴት ዕድለኛ ነሽ” ሲሉ፣ ዕድል ሳይሆን ከእርሱ የተቀበልነው ተዓምር መሆኑን በመመስከር የመልካም ስጦታ ትክክለኛው ምንጭ የሆነውን እግዚአብሔርን እንዲያዩ መንገድ እንክፈት። 

“ታውቁና ታምኑብኝ ዘንድ፣ እርሱ እኔ እንደሆንሁ ትረዱ ዘንድ፣ እናንተ ምስክሮቼ፣ የመጥሁትም ባሪያዬ ናችሁ”

በኢሳይያስ 43፡10

 

Hanna Arayaselassie

Hanna is a "servant of the people" with a big heart for Ethiopia and its ever-growing prospects. She enjoys hosting, charades, and inviting conversations that start with, "Tell me everything about you and your life!"

white-200.png

Serving Ethiopian women by encouraging and exemplifying vulnerable, thought-provoking conversations around the Gospel of Jesus Christ, the mission of the
Church, and the life of a Christian.

Address
:
Golagul Tower
Addis Ababa, Ethiopia

Emailinfo@selahethiopia.org
selahforethiopia@gmail.com

Follow Us

Subscribe to emails from Selah

We have officially launched our website and all our social media platforms. Please join us, follow, and share. Subscribe to our newsletter bringing you regular updates, resources, and everything in between!

Copyright © 2023 Selah Ministries.
Address: Addis Ababa, Ethiopia 
Emailinfo@selahethiopia.org