ጊዜዬን ወደ ማቀዱ ሲመጣ፣ እኔ ብዙ ጊዜ ማኘክ ከምችለው በላይ ከሚነክሱት አንዱ ነኝ። ብዙ ጊዜ ከጓደኞቼ ጋር ለቡና ጊዜ ለመፍጠር፣ ከተቀጣሪነት ስራዎች ጋር፣ ድርጅትን ከማስተዳደር ጋር፣ የግል ጉዳዮችን ለመከታተል እና አገልግሎትን በደንብ ከመምራት ጋር አስማምቼ ለመኖር እሞክራለሁ፣ እና በቀላሉ በጣም ከባድ እና በጣም አስጨናቂ ሊሆን ይችላል። ሩጫው አስጨናቂ ከመሆንም አልፎ ከእግዚአብሔር ጋር ጊዜ ማሳለፍን እንደ ዋና ከማየት ብዙ ጊዜ ያግደኛል።
እግዚአብሔር ግን ለተለያየ አላማ ከተለያየ አይነት ሩጫችን ያስቆመናል። መልዐኩ ገብርኤል ለማርያም “እነሆ፤ ትፀንሻለሽ፤ ወንድ ልጅም ትወልጃለሽ፤ ስሙንም ኢየሱስ ትዪዋለሽ። እርሱም ታላቅ ይሆናል፤ የልዑል ልጅም ይባላል፤ ጌታ አምላክ የአባቱን የዳዊትን ዙፋን ይሰጠዋል፤ በያዕቆብም ቤት ላይ ለዘላለም ይነግሣል፤ ለመንግሥቱም ፍጻሜ የለውም” ሲላት፣ ለራሷ ከዮሴፍ ጋር ያሰበችውን ወይም ያቀደችውን ህይወት እንዲሁም ስለ ወደ ፊት ህይወቷ የነበራትን ሐሳብ አስቁሞታል። ግን ማርያም የህይወቷን አስደንጋጭ መቀያየር አይታ ያደረገችው ነገር እኔም፣ እኛም የምንማርበት ነው። ማርያም አምላኳን ጥያቄ ጠየቀች እንጂ አምላኳን ጥያቄ ውስጥ አላስገባችውም። ማርያም አምላኳን አመነች።
እኔ ከጠቀሱት የአኗኗር ዘይቤ እግዚአብሔር ከጥቂት ቀናት በፊት ፍሬኑ በድንገት እንደተያዘበት መኪና አስቆመኝ። የሰሞኑ ጉንፋን ብዬ ሳላስታምመው እና ስገፋው የነበረው እውነትም ኮቪድ-19 መሆኑ በምርመራ ተረጋገጠ። ከበሽታው በላይ ያስፈራኝ እና ያስደነገጠኝ የማይሰሩት ስራዎቼ፣ የማይተገበሩት እቅዶቼ ነበሩ። ማርያምም ልክ እንደ እኔ ፈርታ እና ደንግጣ ነበር ብዬ አስባለሁ።
እግዚአብሔር ሕይወቴን ሲያቋርጥ፣ መጀመሪያ ጸሎቴ የነበረው በሚገርም ተዐምር አድኖ መልሶ በአንድ ቀን ውስጥ ወደ ፈለኩት ስራ እንዲያሰማራኝ ነበር። ከትንሽ ሰዐታት በኋላ ግን ልክ እንደ ማርያም ላደርግ ወሰንኩ። ማመን አለብኝ። በአሁን ሰዐት ሕይወቴ እንዳሰብኩት ወይም እንደ አቀድኩት ባይሄድም፣ እግዚአብሔር ግን መልካም አላማ እንዳለው አምኜ ቤቴ ተቀመጥኩ። በመቁነጥነጥ እና በመጨነቅ መሀልም ከእርሱ ጋር የተረጋጋ ጊዜ ላሳልፍ ቻልኩ፣ ያ ጊዜ ምን ያህል እንደ ናፈቀኝም አስታወሰኝ። እግዚአብሔር ከእኔ ጋር ጊዜ ለማሳለፍ፣ እኔ ተገቢ የሆነ እረፍት እናዳደርግ እኔን ቤቴ አስቀመጠኝ።
ይህን የምለው ምን ለማለት ነው፤ ልክ እንደ እኔ ከእግዚአብሔር ጋር ያላችሁ ግንኙነት በሕይወት ሩጫ ዋዥቆ እንደሆነ፣ እግዚአብሔር በማመን መጀመር እንችላለን። እግዚአብሔር እኛን ወደ መጠጋት ሊያመጣን፣ ወደ እቅፉ ሊመልስን የታመነ ነው። እግዚአብሔር በህይወታችሁ እንደ እኔ ትልቅ ለውጥ ሳያመጣ ከእርሱ ጋር ያላችሁን የምታድሱበት እና የምትጠብቁበትን መንገድ ማበጀት መልካም ነው። ሆኖም ግን እግዚአብሔር ህይወታችንን ሲያቋርጥ፣ ከምንሮጥበት መንገድ አስቁሞ ከፊት ለፊታችን ሲቆም፣ ረጋ እንበል። እንየው። እንመን።
ጸሎት
ጌታ ሆይ፣ በህይወቴ ውስጥ ብዙ የእኔን ትኩረት የሚፈልጉ ነገሮች እንዳሉ ታውቃለህ፤ እና አንዳንድ ጊዜ ከአንተ እና ከቃልህ ጋር ጊዜ ለማሳለፍ እንቅፋት ይሆንብኛል። አቤቱ ወደ ዕረፍትህ ምራኝ። በሕይወቴ ውስጥ አንተን እንዳስቀድምህ እርዳኝ። ጌታ ሆይ፣ እነዚህ ነገሮች በልቤ ውስጥ ስላንተ ቦታ እንዲወዳደሩ አልፈልግም። ቦታህ ቦታህ ይሁን። አሜን።