ለረጅም ጊዜ፣ እኔ እና እግዚአብሔር በግንኙነታችን ውስጥ የት እንዳለን በትክክል ለመለካት በተሰማኝ ስሜት ላይ እተማመን ነበር። ደስተኝነት እና ሰላም ከተሰማኝ እሱ በእርግጥ ቅርብ መሆን አለበት እላለሁ። ብቸኝነት፣ ጥፋተኝነት ወይም ባዶነት ከተሰማኝ፣ እሱ በእርግጥ ፊቱን ከእኔ መልስዋል ብዬ አስብ ነበር።
ያለ ብዙ ማሰላሰል (ወይም መጽሐፍ ቅዱስን ሳላማክር)፣ እግዚአብሔር ስለ እኔ ያለው ስሜት ልክ እንደ እኔው ተለዋዋጭ እንደሚሆን እርግጠኛ ነበርኩ። የመንፈሳዊ ሕይወቴ በደከመባቸው ጊዜዎች ይህ አስተሳሰቤ ትልቁ ውድቀቴ ሆነብኝ። እናም ከእግዚአብሔር ጋር ያለኝ ግንኙነት አስገዳጅ ፣ ወይም ጨርሶ የሌለ እና አልፎ ተርፎም የሚያም ይሆን ነበር። በደከምኩኝ ጊዜ፣ ይህ ማለት በእርግጠኝነት አንድ ከባድ አውዳሚ ነገር አድርጌ መሆን አለበት፣ እናም እግዚአብሔር፣ ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ፣ መዳኔን ሽሮ እንደ ልጁ ነቅፎኛል ብዬ አስባለሁ። እነደዚህ አይነት ወቅቶች በተለያዩ ምክንያቶች በህይወታችን ውስጥ ይመጣሉ እና ይሄዳሉ ። በእነዚህ ጊዜያት እግዚአብሔር ቅርብ ነው ብሎ ለማሰብ ከባድ ነው። ነገር ግን እንደ ጌታችን ልደት ይህንን የእግዚአብሔር ቅርበት እውን ሊያደርግልን የሚችል ነገር የለም።
ለካስ እግዚአብሔር ከእኔ እና ከእናንተ ጋር ሕብረትን እጅግ ይሻል! ይህን ህብረት ለዘለአለም ለማረጋገጥም አንድያ ልጁን ላከ (እኔ በሐጢያት እየተደነቃቀፍኩ እንደምኖር አስቀድሞ ቢያውቅም፣ እንደዚህ አይነት ከእርሱ ጋር የመራራቅ ጊዜን እንደማሳልፍ አስቀድሞ ቢያውቅም፣ መንፈሳዊ ሕይወቴን ቸል የምልባቸው ጊዜዎች እንደሚኖሩ ቢያውቅም፣ እርሱን ለማስከበር ብፈጠርም ራሴን ላስከብር የምጥርባቸው ጊዜዎች እንደሚበዙ ቢያውቅም፣ በአጠቃላይ ስለ እኔ ማንነት በርብሮ ቢያውቅም)። እግዚአብሔር ከእኔ ጋር ሕብረትን የፈለገው እኔ ከመፈጠሬም በፊት ነው፣ ገና በገነት ሰውን ሲያስቀምጥ ጀምሮ ይህ የሕብረት ፍላጎቱ ነበረ። በአዳም እና ሔዋን ጥፋት ያልተለወጠው ይህ ፍላጎቱ፣ በእኔ ማንነት በፍጹም አይለወጥም። እግዚአብሔር ቅርብ ነው፣ ከእኔ ጋር ቅርበትንም ይሻል። ይህን እውነት ሊሽር የሚችል ምንም ነገር የለም።
ይህ የገና በዐል በቀረበ ጊዜ እናም የጌታን ውልደት በምናሰላስልበን ጊዜ ይህን እናስታውስ፤ እግዚአብሔር ለሕብረት ያለው ፍላጎት ስጋ ለብሶ በመሀላችን ነበረ። ሰይጣን ያላሸነፈው፣ ሀጢያት ያላባረረው፣ የሰው ድክመት ያላደከመው የእግዚአብሔር ሕብረት ፍላጎት ዛሬም ይኖራል።
ጸሎት
እግዚአብሔር ሆይ፣ ታማኝ አምላክ ስለሆንክ አመሰግንሀለሁ። እኔ ከሚሰማኝ መራራቅ ይበልጥ ያንተ የማይናወጥ ቃል “ከቶ አልተውሽም፣ በፍፁም አልጥልሽም“ ሲል ሊታመን ይገባል። ሁሉን ቻይ እግዚአብሔር ሆይ፣ ስሜቴን ወይም ሁኔታዬን ከማዳመጥ ይልቅ አንተን እንዳዳምጥ እርዳኝ፣ ወደ ራስህም እና ወደ ቃልህም ጥራኝ። አንተ መቼም ከእኔ ልትርቅ እንደማትሻ እንዳውቅ እና እንዳምን እባክህ እርዳኝ። ስምህ ከዘለአለም እስከ ዘለአለም የተባረከ ይሁን።
ወደ ልጁ፣ ወደ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ኅብረት የጠራችሁ እግዚአብሔር የታመነ ነው።
1 ቆሮንቶስ 1:9