ሕፃን ተወልዶልናልና፤
ወንድ ልጅ ተሰጥቶናል፤
አለቅነትም በጫንቃው ላይ ይሆናል።
ስሙም፣ ድንቅ መካር፣
ኀያል አምላክ፣
የዘላለም አባት፣ የሰላም ልዑል ይባላል።
ኢሳይያስ 9፥6-7
ይህ የህይወቴ ወቅት ለጥበብ፣ ለማስተዋል ልመና የተሞላ ነው። ጥበብ ለራሴ፣ ጥበብ ለወዳጆቼ፣ ጥበብ ለመሪዎቼ እና ጥበብ ለማልስማማቸው ሰዎች።
የእኔ ኑዛዜ ግን ጥበብን እፈልገዋለሁ እንደምለው መጠን እየፈለኩት እንዳልሆነ ነው።
ከአመታት በፊት፣ አንድ የ17 አመት ልጅ ለምክር ወደ እኔ መጣች እና “ስለዚህ ጉዳይ ከጓደኞችሽ ጋር ተነጋግረሻል?” ስል ጠየቅኳት። እሷም “አይ፣ እኔ ከማውቀው ሌላ ምን ይነግሩኛል? የእነሱ እና የእኔ ጥበቦች ተመሳሳይ ናቸው ስለዚህ በትክክለኛው መንገድ ይመሩኛል ብዬ አላስብም" አለችኝ። በህይወታችን ውስጥ ከሰዎች ምሪት ስንፈልግ፣ አንድአንድ ጥያቄዎችን እንጠይቃለን፣ አይደል? "ትሰማኝ ይሆን?" "ትረዳኝ ይሆን?" "ከዚህ በፊት ተመሳሳይ ነገር አጋጥሟታል?" “ያኔስ ትግሉን አሸንፋለች?“ "የእኔን ምስጢሮች ለመጠበቅ ታማኝ መሆን ትችላለች?" "ሂደቱን በምረዳበት መንገድ ትመራኛለች?" "ፕሮፌሽናል ነች?" እና ሌሎችም ብዙ እንጠይቃለን።
ከጓደኞች፣ ቤተሰብ፣ ፓስተሮች፣ ሙያዊ አማካሪዎች እና የንግድ እና የአስተዳደር አማካሪዎች መመሪያ ስንፈልግ፣ ውስንነታቸውን ቶሎ እንማራለን። የገና በዓል እየተቃረበ ሲመጣ፣ አስደናቂው መካሪ የሆነውን ኢየሱስን ኢሳይያስ 9:7ን እንድትመለከቱ ላበረታታችሁ እወዳለሁ። የኢየሱስ ምክር፣ መመሪያ ወይም ማጽናኛ በምንፈልገው የሕይወት ዘርፍ ውስጥ ሁሉ በሙላት መገኘት ይችላል፣ ይገኛልም። የእርሱ ጥበብ ምንም ገደቦች የሉትም። ሁሉን የሚያውቅ እና ኃያል የሆነውን አምላክ እንደ አማካሪ ማግኘታችን ለእኛ እጅግ ልዩ ነው። እሱ ሁል ጊዜ እኛን ለማዳመጥ አለ። ጸሎት በዚህ ድንቅ አማካሪ የምንደመጥበት፣ የስነ ልቦና ማማከሪያ ክፍላችን ነው። መጽሐፍ ቅዱስ በሕይወታችን ውስጥ ለእያንዳንዱ ሁኔታ መመሪያ የምናገኝበት የሕክምና መመሪያችን ነው። አትሳሳቱ፣ መጽሐፍ ቅዱስ መመሪያ ብቻ ሳይሆን ጥንካሬ የምንቀዳበትም ቦታ ነው።
በቅርቡ ገናን ለማክበር ስንጠብቅ፣ ኢየሱስ እንደ አማካሪ ማን እንደሆነ በማሰብ ሁላችንም እንድንጽናና አበረታታለሁ። እሱ ድንቅ ነው፤ ምርጥ፣ አንደኛ ደረጃ፣ አስደናቂ፣ ተወዳዳሪ የሌለው፣ ያልተለመደ፣ ከፍ ከፍ ያለ፣ ታላቅ መካሪ። ወዳጆች፣ እርምጃችሁን ያውቃል፣ የምታልፉትን ማዕበል ይረዳል። ከሱ እንድትሰሙ እና እናንተም እንድትሰሙ ትንሽ ቀረብ በሉ፣ ተጠጉም። ጸሎት የምንደመጥበት፣ እኛም የምናደምጥበት መንገድ ነው። ቃሉ የእርሱን መንገዶች የምንማርበት ነው። በጸሎት ለመቅረብ ለብቻችን ማድረግ ካቃተን፣ ከጓደኛ እርዳታ እንጠይቅ። እርሱም እንዲረዳን እንጠይቀው።
ጸሎት
ጌታ ሆይ፣ አንዳንድ ጊዜ ብቻዬን እንደሆንኩ ቢሰማኝም እና ብዙ ጥያቄዎች በውስጤ ቢነሱም፣ እባክህ ሁሌም ከእኔ ጋር እንዳለህ እና በዘላለማዊ ፍቅር እንደተወደድኩ አስታውሰኝ። ይህንን ለራሴም ሳልረሳ በልቤ ተተክሎ፣ በቃልህ ውሀ ሁሌ የሚለመልም እውነት ይሁንልኝ። ለሌሎችም ያንተን መዐዛ ሽታ የማቀምስ ሰው አድርገኝ። አሜን