ኢየሱስ የተወለደበት ጊዜ ሁሉም ነገር መልካም የነበረበት ጊዜ አልነበረም። እግዚአብሔርን በሚወዱ እና በሚፈሩ ሰዎች ሕይወት ውስጥ ብዙ ግራ መጋባት እና ያልተጠበቁ ነገሮች የሚከሰቱበት ጊዜ ነበር። በተመሳሳይ ሁኔታ እግዚአብሔርን እየፈራንና እየተከተልን ላለን በሕይወታችን ውስጥ እየታዩ ያሉ ብዙ ነገሮች አሉ። በየእለቱ የሚያጋጥሙን ጥርጣሬዎች፣ ስለ ነገሮች ያለንን ግንዛቤ መቀየር ማስፈለጉ እና በዛው ልክ ደግሞ ሁሉም ነገር የሚቀያየርበት ፍጥነት ሊያስደንቀን፣ ሊያስደነግጠን ይችላል። ለአንዳንዶቻችን ደግሞ ከነገሮች ጋር በፍጥነት ታርቆ ለመስተካከል ጥሩ ላልሆንን ውጥረቱ እጥፍ ድርብ ነው። የአለም ጭንቀት ብዙ ነው፣ በውስጣችን የምትፈጥረውም ጥያቄ በጣም ብዙ ነው።
ብቻችንን ስላልሆንን ግን እግዚአብሔር ይመስገን። በስሜት ግርግር እና እርግጠኛ ባልሆኑ ሁኔታዎች ውስጥ እንኳን እግዚአብሔር ከእኛ ጋር ነው። በዚህች የፍቅር እና የጽድቅ በረሀ በምትመስለን አለም፣ ወዳጃችን ኢየሱስ አብሮን ይራመዳል። እሱ የለም ብለን በምናስብባቸው ጊዜያት እንኳን እርሱ አለ። እርሱ እኛን ሊመራን፣ ሊያጽናናን፣ ሊገሥጸን እና ሁል ጊዜ ሊወደን አለ።
በሚቀጥለው ጊዜ ብቻችንን እንደሆንን ሲሰማን (ያ ጊዜ ደግሞ መምጣቱ አይቀርም)፣ ወደ እግዚአብሔር ቃል እንሩጥ። እርሱ ባሳየን ፍቅር ራሳችንን እንሰውር፤ እኛ እርሱን ከመውደዳችን በፊት ወዶናልና።
በህይወትሽ የትም ብትሆኝ በዚህ ተጽናኚ፣ ኢየሱስ እኛን ለማዳን ከሰማይ መጣ። እኛን ከአለም ለማዳን፣ ከራሳችንም ለማዳን እና ከባርነት ለመቤዠት ለእኔ እና ለአንቺ ሲል መጥቷል። ስለዚህ እርሱ ለእኛ ያለውን ፍቅር ለራሳችን እናውጅ። ወደር የለሽ ዋጋ እንዳለን ለራሳችን እንንገር፤ የምናደርገው ወይም የማናደርገው ነገር በህይወታችን ውስጥ ምንም የማንነት መለኪያ እንደማይሰጠን ኢየሱስ አርጋግጦናል። ዋጋ፣ ማንነት፣ እና ሙሉነት በእርሱ ብቻ ነው። ስለዚህም በማንኛውም ሁኔታ የእግዚአብሔርን ልጅ ኢየሱስን እናክብረው፣ በልባችንም ከፍ እናድርገው። አማኑኤል - እግዚአብሔር ከእኛ ጋር!
ጸሎት
ጌታ ሆይ፣ አንዳንድ ጊዜ ብቻዬን እንደሆንኩ ቢሰማኝም እና ብዙ ጥያቄዎች በውስጤ ቢነሱም፣ እባክህ ሁሌም ከእኔ ጋር እንዳለህ እና በዘላለማዊ ፍቅር እንደተወደድኩ አስታውሰኝ። ይህንን ለራሴም ሳልረሳ በልቤ ተተክሎ፣ በቃልህ ውሀ ሁሌ የሚለመልም እውነት ይሁንልኝ። ለሌሎችም ያንተን መዐዛ ሽታ የማቀምስ ሰው አድርገኝ። አሜን